(ባህርዳር፣ ጥቅምት 17/2018 ዓ.ም) “በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ ፬” በሚል መሪ ቃል በሀገር አቀፍ ደረጃ ሲካሄድ የቆየው የ2017 የክረምት ወራት የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ማጠናቀቂያ እና የእውቅና መርሐ ግብር ተካሄደ፡፡
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በመርሐግብሩ እንደገለፁት በ2017 የክረምት ወራት የበጎ ፍቃድ አገልግሎት 53 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ የህበረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል።
በአገልግሎቱም በመንግስትና በማህበረሰቡ ያልተሸፈኑ ከ56 ቢሊዮን ብር በላይ የሚገመት የልማት ሥራዎችንና ማህበራዊ አገልግሎቶችን ማከናወን መቻሉንም ተናግረዋል።
የበጎ ፈቃድ እንቅስቃሴ በሀገራችን የወጣቶችን እና የሴቶችን ሁለገብ ተሳትፎን ለማጎልበትና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ከሚካሄዱ ተግባራት መካከል አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል።
ይህም በመንግስት እና በህዝብ መካከል ያለውን ትስስር በማጠናከር ድልድይ በመሆን እና እየተዳከሙ የነበሩ ማህበራዊ እሴቶቻችን መልሰው እንዲዳብሩ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል ብለዋል።
በተጨማሪም በክረምቱ ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በህዝብ ዘንድ እንዲሰርጽ እና ከውጤቱም ይበልጥ ተጠቃሚ እንዲሆን የተሰሩ የልማት ስራዎችንም ህብረተሰቡ በባለቤትነት ስሜት እንዲጠብቅ እና እንዲንከባከብም በቅንጅት መሠራቱን ገልፀዋል።
በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደር ዘንድ ሀገራዊ አንድነት እንዲፈጠር ከፍተኛ ሚና መጫወቱን ጠቁመዋል።
አገራችን ኢትዮጵያ አሁን ባለችበት ወሳኝ የለውጥ ምዕራፍ የወጣቶች እና የሴቶች ሚና አስተዋጽኦ እጅግ የላቀ በመሆኑ አሁን ያለውን ለውጥ፣ እድገናት የመደጋገፍ ባህል ቀጣይነት ማረጋገጥ ያስፈልጋል ብለዋል።
በተለይ መጪው ሀገራዊ ምርጫ እንደመሆኑ በጎ ፈቃደኞች በማስተባበር እና ሰላማዊ ምርጫ ምህዳር እንዲፈጠር በማደረግ ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን እና የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።




